በደቡብ ሱዳን በቴሌኮም ዘርፍ አራተኛው የቴሌኮም ኦፕሬተር ሆኖ የተመዘገበው በኢትዮጵያዊ ባለሀብት አቶ አይሸሹም ተካ የተመሰረተው ቴሌ ሞባይል በደቡብ ሱዳን በየ15 አመቱ የሚታደስ የ 30 አመት ፍቃድ አንደደተሰጠው ስራ አስኪያጁ አቶ አንዷለም አድማሴ ዛሬ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል።
“በውጭ ሀገር ኢትዮጵያዊን በማሰማራታችን ኩራት ይሰማናል። ለደቡብ ሱዳን አገለግሎት በመስጠት ፣የስራ እድልና ገቢ ለማስገኘት እንዲሁም ለውዷ ሀገራችን ዶላር ለማስገኘት እንሰራለን “

“ደቡብ ሱዳን የገባነው አራተኛ የቴሌኮም ኦፕሬተር ሆነን ነው ። ፋይበር ኦፕቲክስ በመጨመር ፈጣን የኢንተርኔት አገልግሎት እንሰጣለን ። ደቡብ ሱዳን ካላት 12 ሚልየን ህዝብ አብዛኛውን የእኛን ቴሌኮም እንዲጠቀም እናደርጋለን” ብለዋል።
አቶ አንዷአለም ባለ ሀብቱን አቶ አይሸሹም ተካንን አድነቃዋል።
” አቶ አይሸሹም ደቡብ ሱዳንን በደንብ ያውቃታል ። በቴሌ ዘርፍ ብሰማራ ብሎ ማንም ኢትዮጵያዊ በሌላ ሀገር ያልደፈረውን ለመስራት አቅዶ ተነስቷል።ይሄ ሌሎች ኢትዮጵየዊ ባለሀብቶች ተመሳሳይ ስራ እንዲሰሩ በር ከፋች ነው። እኔም ኢትዮ ቴሌኮም የነበረኝን ልምድ ጨምሬ ከደቡብ ሱዳን ባለሙያዎች ጋር ሌሎች ኢትዮጵያውያንም አካትቼ የአቅሜን ለመስራት ተዘጋጅቻለው ። ውጤትም አመጣለው ብዬ ተስፋ አድርጋለው ” ሲሉ ተናግረዋል።
አቶ አንዱአለም አክለው በደቡብ ሱዳን ያለው የሰላም ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ እንደመጣ ገልፀው ይሄም ለኢንቨስትመንት ጥሩ መደላድል ይፈጥራል ብለዋል።